‹ሶላትን መስገድ የፈለጋችሁ ጊዜ ሰልፋችሁን አስተካክሉ። ከዚያም አንድ ሰው ይምራችሁ። ኢማሙ ተክቢራ ያደረገ ጊዜ እናንተም ተክቢራ አድርጉ!
Choose an available translation of this Hadeeth
Hadeeth text
ከሒጥጧን ቢን ዐብደሏህ አርረቃሺይ እንደተላለፈው እንዲህ ብሏል: "ከአቡ ሙሳ አልአሽዐሪይ ጋር ሶላትን ሰገድኩ። ልክ ተሸሁድ ላይ የደረሱ ጊዜም ከሰዎች መካከል አንድ ሰውዬ 'ሶላት ከበጎነትና ከዘካ ጋር ተቆራኘች።' አለ። አቡ ሙሳ ሶላቱን አጠናቆ አሰላመተና ወደ ሰዎች በመዞር 'እንዲህ እንዲህ የሚል ንግግር የተናገረው ማነው?' አለ። ሰዎቹም ዝም አሉ። በድጋሚ 'እንዲህ እንዲህ የሚል ንግግር የተናገረው ማነው?' አለ። አሁንም ሰዎቹ ዝም አሉ። አቡ ሙሳም 'ሒጧን ሆይ! አንተ ነህ መሰለኝ ይህን የተናገርከው?' አለኝ። ሒጧንም 'እኔ አላልኩም! በሷ ምክንያት ትወቅሰኛለህ ብዬ እኔም ፈርቼ ነበር።' አለ። በዚህ ወቅት ከሰዎቹ መካከል አንድ ሰውዬ 'እኔ ነኝ ያልኩት። መልካምን እንጂ ሌላ አልፈለግኩበትም።' አለ። አቡ ሙሳም 'ሶላታችሁ ውስጥ እንዴት እንደምትሉ አታውቁምን? የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ኹጥባ አደረጉ። ለኛ ሱናቸውን ገለፁልን አሰጋገዳችንንም አስተማሩን።' እንዲህም አሉን: ‹ሶላትን መስገድ የፈለጋችሁ ጊዜ ሰልፋችሁን አስተካክሉ። ከዚያም አንድ ሰው ይምራችሁ። ኢማሙ ተክቢራ ያደረገ ጊዜ እናንተም ተክቢራ አድርጉ! ፣ {غَيرِ المَغضوبِ عَلَيهِم وَلَا الضّالّينَ} [አልፋቲሐ:7] ያለ ጊዜ አሚን በሉ አላህ ይቀበላችኋልና፤ ተክቢራ አድርጎ ሩኩዕ ያደረገ ጊዜ እናንተም ተክቢራ አድርጋችሁ ሩኩዕ አድርጉ። ኢማሙ ከናንተ በፊት ሩኩዕ ያድርግ ከናንተ በፊትም ቀና ይበል።› የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህም አሉ "ይህቺ (ኢማሙ ቀና ያለበት ቅፅበት) በዚህች (እናንተ ከኢማሙ ከዘገያችሁበት) ጋር ይካካሳል ፤ ኢማሙ 'ሰሚዐሏሁ ሊመን ሐሚደህ' ያለ ጊዜ 'አላሁመ ረበና ለከል ሐምድ' በሉ። አላህ ይሰማችኋልና። የጠራውና ከፍያለው አላህ በነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) አንደበት 'ሰሚዐሏሁ ሊመን ሐሚደህ' 'አላህ ያመሰገነውን ሰሚ ነው' ብሏልና። ኢማሙ ተክቢራ አድርጎ ሱጁድ የወረደ ጊዜ እናንተም ተክቢራ አድርጋችሁ ሱጁድ ውረዱ። ኢማሙ ከናንተ በፊት ሱጁድ ይውረድ ከናንተ በፊትም ቀና ይበል። የአላህ መልዕክተኛ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) እንዲህም አሉ 'ይህቺ (ኢማሙ ሱጁድ ሲወርድ የቀደማቹ ቅፅበት) በዚህች (እናንተ እርሱ ቀና ሲል በምትዘገዩት ቅፅበት) ይካካሳል።' የምትቀመጡበት በሆነ ወቅት የአንዳችሁ የመጀመሪያ ቃሉ 'አትተሒይያቱ፣ አጥጦይዪባቱ፣ አስሶለዋቱ ሊላሂ አስሰላሙ ዐለይከ አይዩሀን-ነቢዩ ወረሕመቱላሂ ወበረካቱሁ አስሰላሙ ዐለይና ወዐላ ዒባዲልላሂ አስሷሊሒን አሽሀዱ አንላ ኢላሀ ኢለሏህ ወአሽሀዱ አንነ ሙሐመደን ዐብዱሁ ወረሱሉህ' ይሁን። ትርጉሙም 'ክብሮች ባጠቃላይ፣ ጥሩ ነገሮች ባጠቃላይ፣ ሶላቶች ባጠቃላይ ለአላህ የተገቡ ናቸው። አንቱ ነቢይ ሆይ ሰላም፣ የአላህ እዝነትና በረከቱ በርሶ ላይ ይሁን። ሰላም በኛ ላይና በአላህ ደጋግ ባሮች ላይም ይስፈን። ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ አምላክ እንደሌለ እመሰክራለሁ። ሙሐመድም የአላህ ባሪያና መልዕክተኛው መሆናቸውንም እመሰክራለሁ።' ማለት ነው።›"
Explanation
"የሰገዳችሁ ጊዜ ሰልፋችሁን አስተካክሉ፣ ቀጥ በሉ ከዚያም ከመካከላቸው አንዱ ሰዎችን ይምራ። ኢማሙ የመክፈቻ ተክቢራ ያለ ጊዜ እንደርሱ አምሳያ ተክቢራ አድርጉ፤ ፋቲሐን የቀራ ጊዜና {غَيرِ المَغضوبِ عَلَيهِم وَلَا الضّالّينَ} [አልፋቲሐ:7] የሚለው ጋር የደረሰ ጊዜ አሚን በሉ ይህንን ከፈፀማችሁ አላህ ዱዓችሁን ይቀበላችኋልና፤ ኢማሙ ተክቢራ አድርጎ ሩኩዕ ያደረገ ጊዜ እናንተም ተክቢራ አድርጋችሁ ሩኩዕ አድርጉ። ኢማሙ ከናንተ በፊት ሩኩዕ ያደርጋል ከናንተ በፊትም ቀና ይላልና እንዳትቀድሙት። ኢማሙ ወደ ሩኩዕ ሲወርድ የቀደማችሁ ቅፅበት እናንተ ኢማሙ ቀና በሚልበት ቅፅበት ወቅት ሩኩዕ ላይ በመዘግየታችሁ ይካካሳል። ያቺ ቅፅበት በዚህች ቅፅበት ትካካሳለች። በዚህ የናንተም የሩኩዕ ቆይታ እንደርሱ የሩኩዕ ቆይታ ይሆናል። ኢማሙ 'ሰሚዐሏሁ ሊመን ሐሚደህ' ያለ ጊዜ 'አላሁመ ረበና ለከል ሐምድ' በሉ። ሰጋጆች ይህንን ያሉ ጊዜ አላህ ዱዓቸውንና ንግግራቸውን ይሰማቸዋል። ምክንያቱም የጠራውና ከፍያለው አላህ በነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) አንደበት 'ሰሚዐሏሁ ሊመን ሐሚደህ' 'አላህ ያመሰገነውን ሰሚ ነው' ብሏልና። ቀጥሎ ኢማሙ ተክቢራ አድርጎ ሱጁድ የወረደ ጊዜ ተከታዮቹም ተክቢራ አድርገው ሱጁድ መውረድ ይገባቸዋል። ኢማሙ ሱጁድ የሚወርደውም ሆነ የሚነሳው ከነርሱ በፊት ነውና። ያቺ ቅፅበት በዚህች ቅፅበት ትካካሳለች። የተከታዩ (የመእሙሙ) የሱጁድ መጠን እንደ ኢማሙ የሱጁድ መጠን ይሆናል። ለተሸሁድ የተቀመጠ ጊዜ የሰጋጅ የመጀመሪያ ቃሉ እንዲህ ማለት ይሁን: 'አትተሒይያቱ፣ አጥጦይዪባቱ፣ አስሶለዋቱ ሊላሂ'፤ 'ንግስና፣ ዘውታሪነትና ልቅና ሁሉ እንዲሁም አምስቱ ሶላቶችም ለአላህ የተገቡ ናቸው።' 'አስሰለሰሙ ዐለይከ አይዩሀን-ነቢዩ ወረሕመቱላሂ ወበረካቱሁ አስሰላሙ ዐለይና ወዐላ ዒባዲልላሂ አስሷሊሒን' ከሁሉም ነውር፣ መከራ፣ ጉድለትና ብልሽት ሰላም እንዲያደርጋችሁ አላህን ተማፀኑ። ነቢያችንን ሙሐመድ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) በሰላምታ ለብቻ እንነጥላቸዋለን። ከዚያም ከአላህ ሀቆችና ከባሮቹ ሀቆች ያለባቸው ግዴታዎችን በተወጡ የአላህ ደጋግ ባሪያዎች ላይም ሰላም እንዲሰፍን ዱዐ እናደርጋለን። ከዚያም ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ እንደሌለና ሙሐመድም የአላህ ባሪያና መልዕክተኛው እንደሆኑ እንመሰክራለን።"
Benefits
የሶላት ድርጊቶችና ንግግሮች ከነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) የተረጋገጠ መሆኑ የግድ ነው። ለአንድም ሰው በሶላት ውስጥ በሱና ያልተረጋገጠን ቃል ወይም ድርጊት መፈልሰፍ እንደማይፈቀድ እንረዳለን።
ኢማምን መቅደምም ሆነ ከርሱ መዘግየት እንደማይፈቀድ እንረዳለን። ለተከታይ የተደነገገው ኢማምን በድርጊቶች መከተሉ ነው።
ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ዲኑን ለማድረስና ለኡመታቸው የዲን ህግጋትን ለማስተማር የሰጡት ትኩረት መወሳቱን እንረዳለን።
ኢማም ለተከታይ መሪ ስለሆነ ተከታይ ከኢማሙ ጋር በሶላት ድርጊቶች ሊቀድመው፣ እኩል ሊሆንና ሊዘገይ አይፈቀድለትም። በተቃራኒ የመከተሉ ጅማሮ መሆን ያለበት ሊሰራው ወደ ፈለገው ድርጊት ኢማሙ መግባቱን እርግጠኛ ከሆነ በኋላ ነው። ሱናው በሶላት ድርጊቶች ኢማሙን መከተል ነው።
በሶላት ውስጥ ሰልፎችን ማስተካከል መደንገጉን እንረዳለን።
Attribution
Categories
Share hadeeth
Sharing options · 0 Total shares

