እነዚህን ሁለት ጫማዎቼን ያዝና ሂድ! ከዚህ የአትክልት ግቢ ውጪ የምታገኘውን ላኢላሃ ኢለሏህን ከልቡ አምኖበት የሚመሰክርን ሰው በጀነት አበስረው።
Choose an available translation of this Hadeeth
Hadeeth text
ከአቡ ሁረይራ ረዲየሏሁ ዐንሁ -አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና- እንደተላለፈው እንዲህ አሉ፦ «የአላህ መልክተኛ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ዘንድ ተሰባስበን ተቀምጠን ነበር። ከኛ ጋር ከነበሩት መካከልም አቡበከርና ዑመር ነበሩ። የአላህ መልክተኛ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ከመካከላችን ተነስተው ሄዱ። ወደ እኛ ሳይመለሱም ዘገዩ። ከኛ ርቀው ባሉበት ጥቃት ይደርስባቸዋል ብለን በመፍራታችንም ደንግጠን ቆምን። ደንግጨ የተነሳሁት የመጀመሪያ ሰው እኔ ነበርኩኝ። የአላህ መልክተኛን ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ለመፈለግም ወጣሁ። በመፈለግ ሳለሁም ባለቤትነቱ ከአንሷሮች መካከል ለአንድ የበኒ ነጃር ተወላጅ የሆነ የአትክልት ግቢ ጋር ደረስኩ። የመግቢያ በሩን ለማግኘትም አጥሩን ዞርኩት። በሩንም አላገኘሁም። ድንገት ግን ከግቢ ውጪ ከሚገኝ ጉድጓድ ወደ አትክልቱ ግቢ ውስጥ የሚገባ ቦይ አገኘሁ። ሰውነቴን ሸምቅቄ የአላህ መልክተኛ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ዘንድ ገባሁ። እርሳቸውም "አቡ ሁረይራ" አሉኝ። እኔም "አቤት የአላህ መልክተኛ ሆይ!" አልኳቸው። "ምን ሆነህ ነው?" አሉኝ። እኔም "እርሶ በመካከላችን ነበሩ። ከመካከላችን ተነስተው ሄዱና ዘገዩብን። ከኛ ርቀው ባሉበት ጥቃት እንዳይደርስቦት ፈርተን ደነገጥን። መጀመሪያ የደነገጠውም ሰው እኔ ነበርኩኝ። ይህ የአትክልት ግቢ ዘንድ መጣሁ። ቀበሮ ሰውነቱን ሸምቅቆ እንደሚገባውም ሰውነቴን ሸምቅቄ ገባሁ። የተቀሩት እርሶን የሚፈልጉ ሰዎች ከኋላዬ ናቸው።" አልኳቸው። እርሳቸውም "አቡ ሁረይራ ሆይ! … " አሉኝና ሁለት ጫማቸውን ሰጥተው እንዲህ አሉኝ "እነዚህን ሁለት ጫማዎቼን ያዝና ሂድ! ከዚህ የአትክልት ግቢ ውጪ የምታገኘውን ላኢላሃ ኢለሏህን ከልቡ አምኖበት የሚመሰክርን ሰው በጀነት አበስረው።" መጀመሪያ ያገኘሁትም ዑመርን ነበር። እርሱም "ምንድናቸው እነዚህ ጫማዎች?" አለኝ። እኔም "እነዚህ የረሱል ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ጫማዎች ናቸው። እነዚህን ጫማዎች ሰጥተው ከአጥሩ ውጭ ያገኘሁትን ላኢላሃ ኢለሏህን ከልቡ አምኖ የሚመሰክርን ሰው በጀነት እንዳበስረው ልከውኝ ነው።" አልኩኝ። ዑመርም በሁለት እጆቹ ደረቴን መታኝና በመቀመጫዬ ወደቅኩ። እንዲህም አለኝ "ተመለስ አንተ አቡ ሁረይራ" እኔም ወደ አላህ መልክተኛ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- እንባ እየተናነቀኝ ተመለስኩኝ። ዑመርም ከኋላየ ነበር ሳስተውልም እኔን ተከትሎ መጥቷል። የአላህ መልክተኛም ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- "ምን ሆንክ አንተ አቡ ሁረይራ!" አሉኝ። እኔም "ዑመርን አገኘሁት። የላኩኝን ጉዳይም ስነግረው ደረቴ ላይ መቶኝ በመቀመጫዬ ወደቅኩ። ተመለስም አለኝ።" አልኳቸው። የአላህ መልክተኛም ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- "አንተ ዑመር ለዚህ ተግባርህ ምን አነሳሳህ?!" አሉት። እርሱም "እናትና አባቴ ለርሶ ፊዳ ይሁኑና የአላህ መልክተኛ ሆይ! አቡ ሁረይራን ላኢላሃ ኢለሏህን ከልቡ አምኖበት የሚመሰክር ሆኖ ያገኘውን ሰው በጀነት እንዲያበስር ልከውታልን?" አለ። እርሳቸውም "አዎ" አሉ። እርሱም "እንዲህ አያድርጉ። ሰዎች በርሷ ላይ ጥገኛ ይሆናሉ (ይሳነፋሉ) ብዬ እፈራለሁ። ተዉዋቸው ይስሩ።" አለ። የአላህ መልክተኛም ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- "ተዉዋቸው (አትንገሯቸው)" አሉ።»
Explanation
Benefits
አስደሳች በሆነ ወሬ ማበሰር የተደነገገ መሆኑን እንረዳለን።
ኢማን ንግግር፣ ተግባርና እምነት እንደሆነ እንረዳለን።
ቃዲ ዒያድና ሌሎችም ዑለማዎች እንዲህ ብለዋል: "የዑመር ረዲየሏሁ ዐንሁ - አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና - ድርጊትና ነቢዩን -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- መመላለሱ እርሳቸውን ለመቃወምና ትእዛዛቸውን ለመመለስ አልነበረም። ምክንያቱም አቡ ሁረይራን የላኩበት ጉዳይ ለኡማው ቀልብ መልካም ያልሆነና ብስራት የሌለው ሆኖ አይደለም። ዑመር ረዲየሏሁ ዐንሁ ግን ይህን ብስራት መሸሸግ ለኡማው በዚህ ብስራት ላይ ጥገኛ እንዳይሆኑ የተሻለና የተገባ መሆኑን ስላስተዋሉ እንጂ። ይህ ብስራት በዚህ ወቅት ከሚነገራቸው ይልቅ በሚያውቁት ላይ ሆነው መስራታቸው መልካም ነገር ይዞ እንደሚመጣ ተረድተው ነው። ለነቢዩ -የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ይህን ሃሳብ ሲያቀርብላቸውም ተቀበሉት።"
ነወዊይ እንዲህ ብለዋል: "ይህ ሐዲሥ አንድ መሪ ወይም በጥቅሉ ታላቅ የሆነ ሰው አንድን ነገር የተመለከተ ጊዜ ተከታዩ ደግሞ ከርሱ ተቃራኒ በሆነ መልኩ ከተመለከተው መሪው በደንብ እንዲያስብበት ተከታይ የሆነው ሰው ለመሪው ሀሳቡን ማቅረብ እንደሚገባ ያስረዳናል። መሪው ደሞ ተከታዩ የተናገረው ነገር ትክክል መሆኑን ከተገለፀለት ወደ ተከታዩ አቋም ይመለሳል። ያለበለዚያ ደግሞ የቀረበለትን ብዥታ ለተከታዩ ትክክል እንዳልሆነ ያብራራለታል።"
አንዳንድ እውቀቶችን ጉዳት ያመጣል ተብሎ ስለሚፈራ ወይም አለማስተማሩ ጠቃሚ ሆኖ የታየ ጊዜ ማሰራጨት እንደማያስፈልግና ከማሰራጨት መቆጠብ እንደሚፈቀድ እንረዳለን።
ለተውሒድ ባለቤቶች ትልቅ ብስራት እንደሆነና ላኢላሃ ኢለሏህን ከልቡ አጥርቶ እየመሰከረ የሞተ ሰውም ለርሱ ጀነት እንዳለው እንረዳለን።
የዑመርን ረዲየሏሁ ዐንሁ ኃይል፣ ጥበብና የግንዛቤውን ጥልቀት እንረዳለን።
ነወዊይ እንዲህ ብለዋል: "ይህ ሐዲሥ አንድ ሰው ከግቢው ባለቤት ጋር ባለው ወዳጅነት ወይም ከዛ ውጪ ባሉ ምክንያቶች ያለ ባለቤቱ ፍቃዱ ቢገባ ደስተኛ እንደሚሆን ካወቀ ባለቤቱን ሳያስፈቅድም ወደሌላ ሰው ግቢ መግባት እንደሚፈቀድ ያስረዳናል።"
Attribution
Categories
Share hadeeth
Sharing options · 0 Total shares

